Logo
Getu Temesgen
በደቡብ አፍሪካ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ ተከትሎ 130 ናይጄሪያውያን ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ጥያቄ አቀረቡ
#ethiopia | በደቡብ አፍሪካ ውስጥ ህገወጥ ስደተኞችን በመቃወም እየተካሄደ ያለውን ሰልፍ ተከትሎ ቢያንስ 130 የናይጄሪያ ዜጎች ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ መጠየቃቸውን የናይጄሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቢያንካ ኦዱሜግው ኦጁኩ ገለጹ።

እነዚህ ግለሰቦች የናይጄሪያ መንግስት በቅርቡ ባመቻቸው አዲስ የመመለሻ መርሃ ግብር ለመጠቀም የመጀመሪያዎቹ አመልካቾች መሆናቸው ታውቋል።

ባለፈው ሳምንት በፕሪቶሪያ እና በጆሃንስበርግ የተካሄዱት ተቃውሞዎች ህገወጥ ስደተኞች በስራ እድል፣ በጸጥታ እና በመሰረታዊ አገልግሎቶች ላይ ጫና እያሳደሩ ነው በሚል መንግስት ጠንከር ያለ እርምጃ እንዲወስድ የሚጠይቁ ነበሩ።

የስደተኞች መብት ተሟጋች ድርጅቶች በበኩላቸው የውጭ ሀገር ዜጎች ለደቡብ አፍሪካ ኢኮኖሚያዊ ችግሮች እንደ ሰበብ እየቀረቡ መሆኑን ይገልጻሉ።

የናይጄሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኪሚቢ ኢሞሞቲሚ ኢቢንፋ በደቡብ አፍሪካ በዜጎቻቸው ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት አውግዘዋል።

በተለይም በጸጥታ ሃይሎች ተደብድበው ህይወታቸው ያለፈ ሁለት ናይጄሪያውያንን ጉዳይ በተመለከተ መንግስታቸው አስፈላጊውን የህክምና እና የህግ ሰነዶች እንዲሰጡት እንዲሁም ጥፋተኞች ለፍርድ እንዲቀርቡ ጠይቀዋል።

የናይጄሪያ መንግስት በደቡብ አፍሪካ ያለውን ሁኔታ በቅርበት እየተከታተለ ሲሆን በአቡጃ የሚገኙትን የደቡብ አፍሪካ ከፍተኛ ኮሚሽነር ጠርቶ ማብራሪያ ጠይቋል።

በደቡብ አፍሪካ የሚገኙ የናይጄሪያ ዲፕሎማሲያዊ ሚሲዮኖችም ከሀገር ውስጥ ባለስልጣናት ጋር በመተባበር በዜጎቻቸው ላይ ሊደርስ የሚችለውን አደጋ ለመቀነስ እየሰሩ መሆኑ ተገልጿል።
#nigeria #southafrica #migration #africa #protest #foreignaffairs #getutemesgen #getu #ጌጡ #ጌጡተመስገን #addisababa

3 months ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.