Logo
SeledaPost
የህወሓት አመራር ከኤርትራና ከሌሎች ኃይሎች ጋር ፈጠርነው ያሉት ጥምረት "የጥፋት ቀመር ነው" - ጌታቸው ረዳ‼️

​የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ የህወሓት አመራሮች ከኤርትራው የኢሳይያስ አፈወርቂ ሥርዓትና ከሌሎች የፌደራል መንግሥቱን በሚቃወሙ ኃይሎች ጋር የፈጠሩት ጥምረት በትግራይና በመላው አገሪቱ ላይ ታላቅ ጥፋት የሚያመጣ «የጥፋት ቀመር» ነው ሲሉ ኮነኑ።

​አቶ ጌታቸው በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልእክት እንዳመለከቱት፣ የህወሓት አመራር ቀደም ሲል የፌደራል መንግሥቱን ለማፍረስ ከውስጥና ከውጭ ኃይሎች ጋር የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ሲክድ ቢቆይም፣ አሁን ላይ ግን «የማይመለሱበትን ወሳኝ እርምጃ መውሰዱን» እና ወደ ኃይል አማራጭ መሸጋገሩን በአደባባይ እያወጀ ይገኛል።

​ የጥምረቱ ዋና ዓላማ፦ የህወሓት አመራር ዓላማ የምዕራብ ትግራይን ቦታዎች በሰላማዊ መንገድ ማስመለስ ወይም የፕሪቶሪያውን ስምምነት ማስፈጸም ሳይሆን፣ አዲስ አበባ ያለውን የፌደራል መንግሥት በኃይል መገልበጥ ነው ብለዋል።

​የኢሳይያስ አፈወርቂ ሚና፦ በቅርቡ በሸረሪና የተከሰተውን ግጭትና የተማረከውን በርካታ የጦር መሣሪያ እንደ ማሳያ በማቅረብ፣ የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳይያስ አፈወርቂ ትግራይን ከለላ ለማድረግ «ጠቃሚ ሞኞች»ን በመመልመል በትግራይና በአማራ እናቶችና ሕፃናት ላይ ቁማር እየተጫወቱ ነው ሲሉ ከሰውታል።

​ለትግራይ ሰራዊት የቀረበ ጥሪ፦ ሰራዊቱ ሊገድደው የሚገባው የሕዝቡ ህልውና እንጂ ጦርነትን እንደ ጡረታ ማውጫቸው ያደረጉ ጥቂት አካላት አለመሆናቸውን በመገንዘብ «በቃ» ሊላቸው እንደሚገባና የተደቀነውን ስጋት በሰላማዊ መንገድ ብቻ መፍታት እንደሚቻል አሳስበዋል።

​ለፌደራል መንግሥቱ፦ የፌደራል መንግሥቱ ለፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ሙሉ ትግበራ ታማኝ ሆኖ እንዲቀጥልና ተደጋጋሚ ትንኮሳዎች ቢኖሩም ትዕግሥቱን አጠናክሮ የሰላም አማራጮችን ክፍት እንዲያደርግ ጠይቀዋል።

⨳ በድንበር አካባቢ የሚደረጉ የጦር እንቅስቃሴዎችን ለማረጋገጥ የሳተላይትና የመሬት ላይ ክትትል እንዲደረግ፤
⨳ ግጭት የሚቀሰቅሱ ወታደራዊና ፖለቲካዊ አካላት ተጠያቂ እንዲሆኑ፤
⨳ የሲቪሎችን ደህንነት ቅድሚያ በመስጠት ከሁሉም ወታደራዊ ኃይሎች ሙሉ ወታደራዊ ግልጽነት እንዲጠየቅ።

​"በጦርነት ዝግጅት ፊት ዝምታን መምረጥ የጥፋቱ ተባባሪ መሆን ነው" ሲሉ አቶ ጌታቸው መልእክታቸውን አጠናቀዋል።

Seledadotio
Seledadotio
1 day ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.