Logo
YenetaTube
ግብፅ እና ኤርትራ የቀይ ባሕር ጉዳይ የሚመለከተው "የጠረፉን አገራት ብቻ ነው" አሉ

ቀይ ባሕር ላይ የሚደረግ የትራንስፖርት እንቅስቃሴን እና የወደብ ትስስርን የተመለከተ ስምምነት የተፈራረሙት ግብፅ እና ኤርትራ፤ የቀይ ባሕር ጉዳይ የሚመለከተው "የቀይ ባሕር ጠረፍ አገራትን ብቻ" እንደሆነ ገለጹ።
የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ባድር አብዲላቲ እና የግብፅ የትራንስፖርት ሚኒስትር ሌተናንት ጄነራል ከማል አልዋዚር፤ ግንቦት 8 ቀን 2018 ዓ. ም. ከኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር ተወያይተዋል።

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ባድር አብዲላቲ "የቀይ ባሕር አስተዳደር እና ደኅንነት ጉዳይ በዋነኛነት የሚመለከተው የቀይ ባሕር አጎራባች አገራትን ነው" ማለታቸውን መሥሪያ ቤታቸው አስታውቋል።
ቀይ ባሕርን ከሚያዋስኑ የባሕር ዳርቻ አገራት "ብሔራዊ ደኅንነት ጋር ቀጥተኛ ትስስር" እንዳለው በመጥቀስም "የቀይ ባሕር አጎራባች ያልሆነ አካል ቀይ ባሕርን በሚመለከቱ ጉዳዮች መግባት የለበትም" ማለታቸው ተገልጿል።

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ባድር አብዲላቲ "ኤርትራ ቀይ ባሕርን በማስተዳደር ረገድ ያላትን ዓላማ ግብፅ ትደግፋለች። ለቀይ ባሕር አጎራባች አገራት አንድነት እና ሉዓላዊነትም ዕውቅና ትሰጣለች"ብለዋል።
የኤርትራው የማስታወቂያ ሚኒስትር የማነ ገብረመስቀል በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ሁለቱ አገራት የባሕር ላይ የትራንስፖርት ስምምነት የተፈራረሙት "በነጻነት የሚመራ የዓለም አቀፍ የባሕር ትራንስፖርት እንቅስቃሴን መርሕ መሠረት በማድረግ በዘርፉ ትብብርን ለማጠናከር" እንደሆነ ጠቅሰዋል።

የኤርትራ የትራንስፖርት እና ኮምንኬሽን ሚኒስትር አቶ ብርሃነ ተስፋሥላሴ ከግብፅ የትራንስፖርት ሚኒስትር ሌተናንት ጄነራል ኢ/ር ከማል አልዋዚር ጋር ስምምነቱን ፈርመዋል።
የግብፅ የትራንስፖርት ሚኒስትር ሌተናንት ጄነራል ከማል አልዋዚር፤ ካይሮ የአሥመራን የወደብ እና የባሕር ትራንስፖርት ልማት መደገፍ ትሻለች ማለታቸው ተገልጿል።

BBC

17 days ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.