Logo
FIDEL POST NEWS
🇰🇵 የቀድሞው የሰሜን ኮሪያ መሪ አረፉ

የሰሜን ኮሪያ የቀድሞ የሀገር መሪ እና ለኪም ቤተሰብ ቅርብ አጋር የነበሩት ኪም ዮንግ-ናም አረፉ። እሳቸው ያረፉት ሰኞ ሲሆን ዕድሜያቸውም 97 ዓመት ነበር። ለሞታቸው ምክንያት የሆነው ከካንሰር ጋር በተያያዘ በተከሰተ ውስብስብ ችግር ምክንያት የበርካታ የአካል ክፍሎች ሥራ መቋረጥ እንደሆነ ተነግሯል።

አልጀዚራ ይህንን መረጃ ዛሬ የሀገሪቱን የመንግስት ሚዲያ ጠቅሶ ዘግቧል።

የኮሪያ ማዕከላዊ ዜና አገልግሎት እንደዘገበው ከሆነ የ97 ዓመቱ ፖለቲከኛ ሰኞ ዕለት ከካንሰር ጋር በተያያዙ ችግሮች ምክንያት ሕይወታቸው አልፏል።

ኬሲኤንኤ "ጓድ ኪም ዮንግ-ናም ለፓርቲያችንና ለሀገራችን ታሪክ አስተዋፅዖ ያደረጉ የድሮው ትውልድ አብዮተኛ ነበሩ። የክብርት ሕይወታቸውን በ97 ዓመታቸው አጠናቀዋል" ብሏል።

የዜና አገልግሎቱ በተጨማሪም የሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ ኡን ማክሰኞ ጠዋት ወደ ኪም ዮንግ-ናም አስከሬን በመሄድ ሐዘናቸውን ለመግለጽና አክብሮታቸውን ለመስጠት እንደጎበኙ ዘግቧል። የቀብር ሥነ ሥርዓታቸው በሚቀጥለው ሐሙስ ይፈጸማል።

ከሁለት አሥርተ ዓመታት በላይ የሰሜን ኮሪያን ፓርላማ የመሩት ኪም ዮንግ-ናም ከፍተኛ ዲፕሎማት እና ለኪም ቤተሰብ ቅርብ አባል ነበሩ።

ጥልቅና ኃይለኛ ድምፅ የሚያቀርቧቸው የፕሮፓጋንዳ ንግግሮች ይታወቃሉ። ብዙውን ጊዜ በኪም ጆንግ ኡን እና በሟቹ አባታቸው ኪም ጆንግ ኢል ስም የውጭ እንግዶችን ሲቀበሉ ይስተዋሉ ነበር።
9 months ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.