Logo
SeledaPost
የቲቪ ፕሮግራም አቅራቢዋ እና የሶሻል ሚዲያ ተፅዕኖ ፈጣሪዋ ዳናዊት መክብብ ቀርቦባት በነበረው ክስ በነፃ ተሰናበተች።

ዳናዊት ከ ኤቢኤል ኮንሰልታንሲ ሀላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር፣ ቤተልሔም ታደሰ፣ ገሊላ በለጠ እና ቤል ተስፋዬ ከተባሉ ሌሎች ተከሳሾች ጋር የፍትሐብሔር ክስ የተመሰረተባት ከወራት በፊት እንደነበረ ይታወቃል።

ቁጥራቸው 13 የሆኑ ከሳሾች «እነ ዳናዊት ወደ ውጭ ሀገር እንልካችኋለን በማለት ከእያንዳንዳችን 437,000 ብር ከተቀበሉ በኋላ ሳይልኩን ቀርተዋል» በሚል ክስ ለፍርድ ቤት አቅርበውባቸው ነበር።

«የተወሰደብንን ገንዘብ እንዲመለስልን በተለያዩ ጊዜያት የቃል እና የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ ብንሰጣቸውም እና ጉዳዩን በጋራ መግባባት ለመፍታት ጥረት ብናደርግም ተከሳሾች ብሩን ለመመለስም ሆነ ለማስመለስ እንቢተኛ ሆነዋል» ሲሉ ባስገቡት የክስ ዝርዝር ላይ አብራርተዋል።

አያይዘውም «እኛ ከሳሾች ወደዚህ ጉዳይ በሙሉ መተማመን የገባነው አምስተኛ ተከሳሽ የሆነችው ዳናዊት መክብብ ለድርጅቱ የሰራችውን ማስታወቂያ በማመን ነው» ሲሉ በክሳቸው ላይ ጠቅሰዋል።

ለወራት ክሱን ሲመለከት የቆየው የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቦሌ ምድብ 4ኛ የፍትሐብሔር ችሎት ትናንት ሐምሌ 28 ቀን 2018 ዓ.ም በዋለው ችሎት አራቱን ተከሳሾች ጥፋተኛ በመሆናቸው በአንድነት እና በነጠላ ገንዘቡን ሊከፍሉ ይገባል ሲል ውሳኔ የሰጠ ሲሆን፣ አምስተኛ ተከሳሽ ዳናዊት መክብብ «ሥራን የሠራችው የንግድ ፈቃድ አይታ ነው፤ ስለዚህ ልትጠየቅ አይገባም» ከክሱ በነፃ ተሰናብታለች ሲል እንደወሰነ ሰምተናል።

ዘገባው የኢትዮጲካሊንክ ነው::

Seledadotio
Seledadotio
2 days ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.