Logo
Zehabesha
(ዘ-ሐበሻ ዜና) የአውሮፓ ሕብረት ምክር ቤት እ.ኤ.አ. በ2026 በኢትዮጵያ ዜጎች ላይ ጥሎት የነበረውን ጥብቅና ገዳቢ የቪዛ መመሪያ ሙሉ በሙሉ ለማንሳት መወሰኑን በይፋ አስታውቋል ። ይህ ውሳኔ የተላለፈው ማዕቀቡ የተጣለበትን ዓላማና መሬት ላይ ያለውን ተጨባጭ ለውጥ በጥልቀት ከመረመረ በኋላ ነው ።

የአውሮፓ ሕብረት እ.ኤ.አ. በ2022 ባደረገው ግምገማ፣ በሕገ-ወጥ መንገድ አውሮፓ ውስጥ የሚኖሩ የኢትዮጵያ ዜጎችን መልሶ ከመቀበል እና የጉዞ ሰነድ ከማዘጋጀት ጋር ተያይዞ ከኢትዮጵያ መንግስት በኩል የነበረው ትብብር በቂ አይደለም የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሶ ነበር ። ይህንን ተከትሎ፣ የኢትዮጵያ መንግስት በትብብር ዙሪያ አስፈላጊውን ማሻሻያ እንዲያደርግ ለማበረታታት ታስቦ፣ የሕብረቱ ምክር ቤት እ.ኤ.አ. ሚያዝያ 29 ቀን 2024 ባሳለፈው "Implementing Decision (EU) 2024/1341" በተሰኘው መመሪያ መሰረት በቪዛ ሕጉ ላይ የተወሰኑ መብቶችን በጊዜያዊነት አግዶ ቆይቷል ።

በዚህ ማዕቀብ ምክንያት ላለፉት ሁለት ዓመታት በኢትዮጵያውያን ላይ ተፈጻሚ ሆነው የቆዩት ጥብቅ ገደቦች በርካታ ነበሩ። ከእነዚህም መካከል ለቪዛ አመልካቾች የሚቀርቡ የሰነድ ማስረጃዎችን መስፈርት የማላላት መብት መታገዱ፣ ለዲፕሎማቲክ እና ለአገልግሎት ፓስፖርት ባለቤቶች የሚደረገውን የቪዛ ክፍያ ነፃ የማድረግ አሰራር መቋረጡ፣ መደበኛው የቪዛ ማመልከቻ ማቀነባበሪያ ጊዜ ከ15 ቀናት ወደ 45 ቀናት ከፍ እንዲል መደረጉ፣ እንዲሁም ከአንድ በላይ መግቢያ የቪዛ ፈቃዶችን የመስጠት አሰራር መታገዱ በዋነኝነት የሚጠቀሱ ነበሩ ።

የአውሮፓ ሕብረት ኮሚሽን ማዕቀቡ ከተጣለ በኋላ የኢትዮጵያን አፈጻጸም ተከታታይ ግምገማ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን፣ ኮሚሽኑ ባቀረበው የቅርብ ጊዜ የምዘና ውጤት መሰረት ኢትዮጵያ በአውሮፓ ሕብረት አባል ሀገራት ግዛት ውስጥ በሕገ-ወጥ መንገድ የሚገኙ ዜጎቿን ማንነት በመለየት፣ የአደጋ ጊዜ የጉዞ ሰነዶችን በማውጣት እና የመመለስ ሂደቶችን በዘላቂነት በማደራጀት ረገድ ከፍተኛ እና ቀጣይነት ያለው መሻሻል ማሳየቷ ተረጋግጧል ። በዚህም ምክንያት፣ በኢትዮጵያ ላይ የተጣለው የቪዛ ማዕቀብ ከእንግዲህ አስፈላጊ ሆኖ ባለመገኘቱ፣ የሕብረቱ ምክር ቤት ጥብቅ ገደቦችን ጥሎ የነበረውን የቀደመውን መመሪያ ሙሉ በሙሉ የሚያፈርስ አዲስ ሕግ አውጥቷል ።

ይህ አዲሱ የቪዛ ማዕቀብ ማንሻ ውሳኔ ለአባል ሀገራቱ በግል ከተረጋገጠበት እና ማሳወቂያ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ ወዲያውኑ በተግባር ላይ የሚውል ይሆናል ። ይህም በኢትዮጵያውያን ላይ ተጭኖ የነበረውን የቪዛ መጓተት እና ጥብቅ መስፈርቶችን በማንሳት፣ የቪዛ አሰጣጥ ሂደቱ ወደ ቀደመው መደበኛ እና የተቀላጠፈ አሰራር እንዲመለስ ያደርገዋል።

18 days ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.