Logo
EBC
በጋምቤላ ክልል ከ558 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የቆላማ አካባቢዎች የኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት እየተከናወነ ነው
*******************

በጋምቤላ ክልል በቆላማ አካባቢዎች የኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት (LLRP) የማኅበረሰቡን ኑሮ ለመለወጥ የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ ለማስቀጠል በትኩረት እየተሠራ ይገኛል።

የፕሮጀክቱ የጋምቤላ ክልል አስተባባሪ ዶ/ር ቢየል ቢቾክ እንደገለጹት፤ በክልሉ በቆላማ አካባቢዎች የሚኖሩ የማኅበረሰብ ክፍሎችን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ለማሳደግ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው።

በዚህም መሠረት በተያዘው በጀት ዓመት ብቻ ከ558 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የትምህርት፣ የጤና፣ የመስኖ ፕሮጀክቶች እና የመንገድ መሠረተ-ልማትን ጨምሮ የማኅበረሰቡን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል የሚያግዙ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን አስታውቀዋል።

አስተባባሪው አክለውም፣ የአካባቢ ጥበቃ ሥራን ጨምሮ የተፈጥሮ አደጋ ተጋላጭነትን ለመቀነስ የሚያግዙ ተግባራትን ለማጠናከርና ለዜጎች የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማስፋት በቀጣይነት በትጋት እንደሚሠራ ተናግረዋል።

የፕሮጀክቱን የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማና ምክክር መድረክ በበላይነት የመሩት የክልሉ ርዕሰ-መስተዳድር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኡቶው ኡኮት በበኩላቸው፤ በክልሉ ለሚነሱ የልማት ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ በመስጠት የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል ታስቦ በፕሮጀክቱ እየተከናወኑ ያሉ አበረታች ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አሳስበዋል።

በሚፍታህ አብዱልቃድር
#ethiopia #gambella #llrp #lowlanddevelopment #infrastructure

1 month ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.