Logo
Getu Temesgen
የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በጁባ
#ethiopia | የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን ጁባ ከተማ ለሚያካሂደው ዘመናዊ የመኖሪያና የንግድ ቤቶች ግንባታ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን የደቡብ ሱዳን መንግሥት አስታውቋል።

ኮርፖሬሽኑ ግንባታውን ለማከናወን የሚያስችለውን ስምምነት የፈረመ ሲሆን፣ የህንጻ ግንባታ ቦታዎች መረጣ እና ተያያዥ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች አፈጻጸም በግዛቱ የኮንስትራክሽን እና ቤቶች ኮርፖሬሽን በቀረበ የጥናት ሪፖርት አማካኝነት በዝርዝር ተገምግሟል።

ቀደም ሲል በአዲስ አበባ ከተማ የተደረሰውን የመግባቢያ ስምምነት ወደ ተግባር የሚቀይረው ይኸው አዲስ ውል በጁባ ከተማ ተፈርሟል።

ስምምነቱን የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ረሻድ ከማል እና የደቡብ ሱዳን ሴንተራል ኢኳቶሪያል ግዛት አስተዳዳሪ ክቡር ኢማኑኤል አድል ተፈራርመውታል። በዚህም መሠረት ኮርፖሬሽኑ በጁባ ከተማ ዘመናዊ የንግድና የመኖሪያ ሕንጻዎችን የሚገነባ ይሆናል።

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ረሻድ ከማል ከደቡብ ሱዳን መንግሥት ልዩ መልዕክተኛ ክብርት አዱት ኪር ጋር ውጤታማ ውይይት አካሂደዋል።

በውይይቱ መድረክ ላይ በደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያ አምባሳደር ክቡር ደሊል ከድር እና በደቡብ ሱዳን በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች የተሰማሩት ታዋቂው ባለሀብት ዶክተር አይሸሽም ተካ ተገኝተዋል።

በመድረኩ ላይ ክብርት አዱት ኪር ኮርፖሬሽኑ በጁባ ከተማ ለሚያካሂደው የቤት ልማት ፕሮግራም የደቡብ ሱዳን ፌዴራል መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ አጽንኦት ሰጥተው ገልጸዋል።

ይህ የቤት ግንባታ መጀመር በሁለቱ እህትማማች አገራት መካከል ያለውን ጠንካራና ታሪካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው ያላቸውን ሙሉ እምነት በመግለጽ፣ የደቡብ ሱዳን መንግሥት ለስምምነቱ ተግባራዊነት ያለውን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል።

ዋና ሥራ አስፈጻሚው ዶክተር ረሻድ ከማል በበኩላቸው፣ የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው የጋራ ተጠቃሚነትን፣ አብሮነትን እና ወንድማማችነትን መርህ አድርጎ መሆኑን ገልጸው፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን አጠናቆ ግንባታው በይፋ እንደሚጀመር አስታውቀዋል።

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ረሻድ ከማል እና በርሳቸው የሚመራው የሥራ ልዑካን ቡድን ለአራት ቀናት ሲያካሂድ የነበረውን ጉብኝት አጠናቆ ወደ አዲስ አበባ ተመልሷል።
#የፌዴራልቤቶችኮርፖሬሽን #ኢትዮጵያ #ደቡብሱዳን #ጁባ #ቤትልማት #ኮንስትራክሽን #ኢንቨስትመንት #getutemesgen #getu #ጌጡ #ጌጡተመስገን #addisababa

2 months ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.