Logo
YenetaTube
አሜሪካ በነዳጅ አምራቾች ላይ የተጣሉ አንዳንድ ማዕቀቦችን ልታነሳ ነው

የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የመካከለኛው ምሥራቅ ቀውስን ተከትሎ የነዳጅ ዋጋን ለማረጋጋት አስተዳደራቸው በነዳጅ አምራች ሀገራት ላይ የተጣለውን አንዳንድ ማዕቀብ እንደሚያነሱ አስታወቁ።

ፕሬዚዳንት ትራምፕ በማያሚ ፍሎሪዳ በሚገኘው የጎልፍ ክለባቸው ላይ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንደገለጹት፤ በአንዳንድ ሀገሮች ላይ የተጣሉትን ማዕቀቦች የነዳጅ ዋጋ እስኪስተካከል ድረስ እናነሳለን ብለዋል።

አሜሪካ በአሁኑ ወቅት በሩሲያ፣ በኢራን እና በቬንዙዌላ የነዳጅ ዘርፎች ላይ ማዕቀብ የጣለች ሲሆን፤ ትራምፕ የትኞቹ ሀገሮች የማዕቀብ እፎይታ እንደሚደረግባቸው አልገለጹም።

የሪዮተርስ የዜና ወኪል በርካታ ስማቸው ያልተጠቀሰ ምንጮችን በመጥቀስ ሰኞ ዕለት እንደዘገበው ትራምፕ የነዳጅ ዋጋን ለመቀነስ ባቀዱት እቅድ መሰረት በሩሲያ ላይ የተጣሉትን ማዕቀቦች ለማቃለል እያሰቡ መሆኑን አስታውቋል።

የአሜሪካ የግምጃ ቤት ሚኒስትር ስኮት ቤሴንት ባለፈው ሳምንት የነዳጅ ዋጋን ለማረጋጋት ለህንድ የሚሸጠው የሩሲያ ነዳጅ ላይ የተጣለውን ማዕቀብ ለ30 ቀናት እንደሚተዉ አስታውቀዋል።

በጦርነት ሳቢያ ክፉኛ ንሮ የነበረው የዓለም የነዳጅ ዋጋ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በወሰዱት አዲስ አቋም ምክንያት ድንገተኛ ቅናሽ እያሳየ እንደሚገኝ ተመላክቷል።

ይህም የመካከለኛው ምሥራቅ ቀውስ በኋላ ከታየው የ50 በመቶ የዋጋ ጭማሪ አንጻር ትልቅ መረጋጋት የታየበት ነው ተብሏል።

ይሁን እንጂ የሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ መዘጋቱ እና የባህር ትራንስፖርት መቆሙ አሁንም ለዓለም የነዳጅ ገበያ ትልቅ ስጋት ሆኖ ቀጥሏል።

ጋዜጣ_ፕላስ

5 months ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.