Logo
Zehabesha
(ዘ-ሐበሻ ዜና) የፖለቲካ ተንታኙ ጃዋር መሐመድ፣ የዩናይትድ ስቴትስ መንግስት በህወሓት አመራሮች እና በቤተሰቦቻቸው ላይ የጣለው የቪዛ ማዕቀብ በሰሜን ኢትዮጵያ ዳግም ጦርነት እንዳይቀሰቀስ ከማድረግ ይልቅ፣ ወደ ጦርነት የሚያመራውን መንገድ ይበልጥ ሊያፋጥነው እንደሚችል አስጠነቀቁ።

ጃዋር በኤክስ ጻቸው ባሰፈሩት ዝርዝር ትንታኔ እንዳብራሩት፣ በአሁኑ ወቅት ህወሓት 'መዋጋት' ወይም 'እጅ መስጠት' የሚሉ ሁለት ምርጫዎች ብቻ ከፊቱ ተደቅነዋል። የፌደራል መንግስቱ በበጀት ቅነሳ እና ወደ ትግራይ በሚገቡ መሰረታዊ ቁሳቁሶች ላይ በጣለው ከባድ ገደብ፣ እንዲሁም በፓርቲው ውስጥ በተፈጠረው ጥልቅ መከፋፈል እና በህዝቡ ዘንድ እያደገ በመጣው ቅሬታ ምክንያት፣ የህወሓት አመራሮች ከእጅ መስጠት ይልቅ ዳግም ጦርነት መክፈት የፖለቲካ ህልውናቸውን ለማስጠበቅ የተሻለ ዕድል እንደሚሰጣቸው ያመኑ ይመስላል ብለዋል።
በዚህ ዓይነት የህልውና ስጋት ውስጥ ላሉ አመራሮች የቪዛ ክልከላ ማድረግ ተምሳሌታዊ እንጂ ትርጉም ያለው ጫና እንደማይፈጥር እና አመራሮቹ ለፖለቲካዊ ህልውናቸው ሲሉ የልጆቻቸውን እና የቤተሰቦቻቸውን የጉዞ ዕድል መስዋዕት ከማድረግ ወደኋላ እንደማይሉ ሞግተዋል። ማዕቀቡ ህወሓት የዲፕሎማሲ መንገዶች ሙሉ በሙሉ እንደተዘጋጉበት እንዲያስብ የሚያደርገው እና የጦር ሜዳ ብቸኛ አማራጭ አድርጎ እንዲወስድ ሊገፋፋው እንደሚችል አክለው ገልጸዋል።

ማዕቀቡ ሙሉ በሙሉ በህወሓት አመራሮች ላይ ብቻ ያነጣጠረ መሆኑን የነቀፉት ጃዋር፣ የፌደራል መንግስቱ ወደ ትግራይ እያደረገ ያለው ወታደራዊ ስምሪት እንዲሁም ከፍተኛ የጦር አዛዦች እና ባለስልጣናት እያሰሙት ያለው የጦርነት ቅስቀሳ በአሜሪካ መንግስት ዕይታ ውስጥ አለመግባቱ ሚዛናዊነት የጎደለው መሆኑን አንስተዋል። የዋሽንግተን ውሳኔ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን መንግስት ይበልጥ በድፍረት እና በአግላይነት እንዲንቀሳቀስ የሚያበረታታ መሆኑንም አስገንዝበዋል። ፕሪቶሪያን ለማስፈጸም የሸሹት አሜሪካ እና ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ፣ አሁን ላይ ምንም ዓይነት ማበረታቻ ሳያቀርቡ በትንሽ ዱላ ብቻ ማስፈራራታቸው የዲፕሎማሲውን መንገድ እምነት አልባ እንዳደረገው ጠቁመዋል።

"አሜሪካ ለጣለችው ማዕቀብ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ለዶናልድ ትራምፕ ምን ቃል ገብተው ወይም ምን አቅርበው ይሆን?" ሲሉ የጠየቁት ጃዋር፣ ትራምፕ ከግብፁ ፕሬዝዳንት አብዱልፈታህ አል-ሲሲ ጋር ባደረጉት ስብሰባ ላይ የተናገሩትን ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ኢትዮጵያውያን በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ የሚደረጉትን ነገሮች በቅርበት ሊከታተሉ እንደሚገባ አሳስበዋል።

21 hours ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.