Logo
Zehabesha
(ዘ-ሐበሻ ዜና) የታወቁት የኢኮኖሚ ተንታኝ አቶ ክቡር ገና "Who Should Own Ethiopia’s Gold? The IMF’s Dangerous Advice" (የኢትዮጵያ ወርቅ የማን መሆን አለበት? የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት አደገኛ ምክር) በሚል ባወጡት አዲስ የሞጋች ሀሳብ ጽሑፍ፣ የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ከወርቅ ገበያ አሠራር በሂደት እንዲወጣ የሰጠውን ምክር በጥብቅ ተቃወሙ። ተንታኙ የብሔራዊ ባንክ ከወርቅ ገበያ መውጣት አገራዊ የኢኮኖሚ ልዑላኔንና የውጭ ምንዛሬ ማከማቸት አቅምን አደጋ ላይ የሚጥል አደገኛ አካሄድ እንደሆነ ገልጸዋል።

ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) በቅርቡ ባወጣው የብድር ክለሳ ሪፖርቱ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የወርቅ ገበያ አሠራሩን ማሻሻልና በሂደት ከወርቅ ገበያ ገዢነት በሙሉ በመውጣት ቦታውን ለግል ንግድ ባንኮች መልቀቅ እንዳለበት አሳስቧል። አይ ኤም ኤፍ ይህን ያለው ማዕከላዊ ባንኮች መደበኛ የሸቀጥ ነጋዴ መሆን የለባቸውም በሚል የኢኮኖሚ ንድፈ-ሐሳብ መሠረት ቢሆንም፣ አቶ ክቡር ገና እንደሚሞግቱት ግን ይህ ምክር የበለጸጉና የዳበረ የፋይናንስ ሥርዓት ያላቸውን እንደ ስዊዘርላንድና ካናዳ ያሉ አገራትን ታሳቢ ያደረገ እንጂ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እጥረት ውስጥ ለምትገኘው ኢትዮጵያ ፈጽሞ የማይሰራና አደገኛ ነው። ወርቅ ለኢትዮጵያ ተራ የንግድ ሸቀጥ ሳይሆን የአገሪቱን የውጭ ምንዛሬ የመጠባበቂያ ክምችት የሚያጠናክር፣ አስፈላጊ የነዳጅና የመድኃኒት ግዢዎችን የሚሸፍን እና የአገሪቱን የፋይናንስ ሕልውና የሚያስጠብቅ ስልታዊ አገራዊ ሀብት ነው።

አይ ኤም ኤፍ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክን በግል ንግድ ባንኮች ለመተካት የሚያቀርበው መሬት የማይነካ መላምት የግል ባንኮችን እና የብሔራዊ ባንክን መሠረታዊ ዓላማ ያላገናዘበ መሆኑንም ተንታኙ ያብራራሉ። የግል ንግድ ባንኮች የሚሰሩት ለባለአክሲዮኖቻቸው ትርፍ ለማብዛት ሲሆን፣ ቅድሚያ የሚሰጡትም ለወለድና ለአገልግሎት ክፍያ እንጂ ለአገራዊ የኢኮኖሚ ልማት አይደለም። በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የተቋቋመው የአገሪቱን ገንዘብ ዋጋ ለማስጠበቅ፣ የውጭ ምንዛሬ ክምችት ለማሳደግ እና የአገሪቱን የረጅም ጊዜ የልማት ፍላጎቶች ለማረጋገጥ በመሆኑ፣ የአገሪቱን ዋና የውጭ ምንዛሬ ምንጭ ለግል ባንኮች አሳልፎ መስጠት አገራዊ የኢኮኖሚ ጥቅምንም አሳልፎ መስጠት ነው።

በተጨማሪም አይ ኤም ኤፍ ብሔራዊ ባንክ ከዓለም አቀፍ የወርቅ ዋጋ በላይ ጨምሮ ከአገር ውስጥ አምራቾች ወርቅ መግዛቱን እንደ ገበያ ማዛባት ቢነቅፈውም፣ አቶ ክቡር ገና ግን ይህ አሠራር ተግባራዊና አስፈላጊ መሆኑን ይሞግታሉ። ብሔራዊ ባንክ እየተወዳደረ ያለው ድበር ተሻጋሪ ከሆኑ የኮንትሮባንድ መረቦች ጋር በመሆኑ፣ ተጨማሪ ዋጋ ከፍሎ ወርቁን ወደ መደበኛው የሕግ አሠራር ማስገባት ካልቻለ አገሪቱ ወርቁንም፣ የውጭ ምንዛሬውንም ሆነ የታክስ ገቢዋን ሙሉ በሙሉ ታጣለች።

አቶ ክቡር ገና በጽሑፋቸው ማጠቃለያ ላይ እንዳሰመሩበት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የወርቅ ግዢ አሠራሩን ግልጽ ማድረግና ማዘመን አለበት እንጂ ከገበያው መውጣት የለበትም። ኢትዮጵያ አሁንም የውጭ ምንዛሬ እጥረት ያለባት፣ የኢንዱስትሪ ሽግግሯ ያልተጠናቀቀ እና የኢኮኖሚ ልዑላኔዋ በግንባታ ላይ ያለች አገር በመሆኗ፣ በዚህ ሁኔታ ውስጥ አገሪቱ ያላትን ብቸኛ ስልታዊ የወርቅ ሀብት ቁጥጥር አሳልፋ እንድትሰጥ የቀረበው የምክር ሀሳብ ልማታዊ ሳይሆን ወደኋላ ማፈግፈግ እንደሆነ በመግለጽ ደምድመዋል።

13 days ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.