Logo
FastMereja
ሀምበርግ ላይ በብቸኝነት የተገኙት ኢትዮጵያዊቷ ቤዛ በሻህ የአለምአቀፉን ማህበረሰብ አሳሰቡ‼️

የሆፕ ስፓይና ቢፊዳ እና ሃይድሮሴፋለስ (HOPE-SBH) ዋና ስራ አስኪያጅ የሆኑት ወ/ሮ ቤዛ በሻህ ኃይሌ፣ በጀርመን ሀምበርግ በተካሄደው የ2026ቱ የሃምበርግ ዘላቂ ልማት ኮንፈረንስ (Hamburg Sustainability Conference - HSC) በመገኘት በነርቭ ዘንግ አፈጣጠር ችግሮች መከላከል ዙሪያ ዓለም አቀፍ ትኩረት እንዲሰጥ ጥሪ አቀረቡ።

የሃምበርግ ዘላቂ ልማት ኮንፈረንስ በአለም አቀፍ ደረጃ እየጨመረ የመጣውን የጂኦፖለቲካዊ ውጥረት በመሻገር፣ በፖለቲካ፣ በቢዝነስ፣ በሳይንስ እና በሲቪል ማህበረሰብ መሪዎች መካከል አዳዲስ ስምምነቶችን እና አጋርነቶችን ለመፍጠር የተቋቋመ ዓለም አቀፍ መድረክ ነው። ወ/ሮ ቤዛ በኮንፈረንሱ ማዕቀፍ ውስጥ፣ ከጀርመን የኢኮኖሚ ትብብር እና ልማት ፌዴራል ሚኒስትር ወ/ሮ ሬም አላባሊ-ራዶቫን (Reem Alabali Radovan) ንግግር በመቀጠል ዋና ንግግር አድርገዋል።

ወ/ሮ ቤዛ በንግግራቸው ወቅት፣ በሕይወት የመጀመሪያዎቹ 1,000 ቀናት ላይ የተመጣጠነ ምግብን ለማረጋገጥ የሚደረግ ኢንቨስትመንት የእናቶችንና የሕጻናትን ጤና ለማሻሻል ወሳኝ ስትራቴጂ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። በአለም አቀፍ መድረኩ ላይ፤ "ከእያንዳንዱ የምግብ እጥረት አኃዛዊ መረጃ ጀርባ የሚሰቃዩ ሕፃናት እና ቤተሰቦች መኖራቸውን ማስታወስ ይገባል" ብለዋል። በተጨማሪም "የተደበቀ ረሃብ" በመባል የሚታወቀው የንጥረ-ነገር እጥረት (micronutrient deficiencies) በእናቶች እና በሕፃናት ላይ የሚያደርሰውን ዘላቂና ከባድ ተጽዕኖ በዝርዝር አስረድተዋል። ከዚህም ባለፈ፣ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ግለሰቦችን ከመጉዳት በተጨማሪ ለሰው ልጆች ካፒታል፣ ለኢኮኖሚ ዕድገት እና ለዘላቂ ልማት ትልቅ እንቅፋት እንደሚሆን አብራርተዋል። በሕይወት የመጀመሪያዎቹ 1,000 ቀናት የሚደረግ ኢንቨስትመንት ከጤናም በተጨማሪም ለትምህርት ጥራት፣ ለኢኮኖሚ ምርታማነት እና ለዘላቂ ልማት ግቦች ስኬት መሠረት መሆኑን አስገንዝበዋል።

ይህንን አሳሳቢ ችግር ለመቅረፍም፣ ድርጅታቸው ሆፕ ኤስ.ቢ.ኤች (HOPE-SBH) ላለፉት 10 ዓመታት በትኩረት የሰራባቸውን ዋና ዋና መፍትሄዎች ጠቁመዋል። በተለይም በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ በመተግበር ላይ የሚገኘውን ምግብን በጠቃሚ ንጥረ ነገሮች የማበልጸግ ሥራ በምሳሌነት በማንሳት፤ በሀገር በቀል ጥናትና ምርምር የታገዘውንና ትልቅ ስኬት ያስመዘገበውን ጨውን በአዮዲን እና በፎሊክ አሲድ በጋራ የማበልጸግ ሂደት (Double Salt Fortification) በልዩ አርአያነት አጉልተው አሳይተዋል። ለዚህ ብሔራዊ የፖሊሲ ስኬት መሳካትም የመንግሥት ተቋማት፣ የልማት አጋሮች፣ የግሉ ዘርፍ እና የሲቪል ማኅበረሰብ በቅንጅት መሥራታቸው ወሳኝ ሚና እንደነበረው ገልጸዋል።

ወ/ሮ ቤዛ በማጠቃለያቸው፣ የሃምበርግ ዘላቂ ልማት ኮንፈረንስ እንደሚያንፀባርቀው ሁሉ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ከአጠቃላይ የፖሊሲ ውይይቶች ባለፈ ተጨባጭና ዘላቂ ውጤት ወደሚያመጡ ተግባራዊ አጋርነቶች መሸጋገር እንዳለበት ጥሪያቸውን አቅርበዋል። በሕፃናት የመጀመሪያዎቹ 1,000 ቀናት የተመጣጠነ ምግብ ላይ ኢንቨስት ማድረግ፣ ከማኅበረሰብ ጤና መሻሻል ባለፈ ለትምህርት ጥራት፣ ለኢኮኖሚ ዕድገት እና ለዘላቂ ልማት ዋነኛ መሠረት መሆኑንም ዳግም አረጋግጠዋል።

1 month ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.