Logo
YenetaTube
ፕሬዝዳንት ጌሌ የ27 ዓመታት የስልጣን ቆይታቸውን አራዘሙ

በስትራቴጂካዊ ስፍራ ላይ የምትገኘው የጅቡቲ ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት እስማኤል ኡመር ጌሌ፣ ትናንት በተካሄደው ሀገራዊ ምርጫ 98 በመቶ የሚሆነውን ድምፅ በማግኘት ለተጨማሪ የስልጣን ዘመን መመረጣቸው ታወቀ።

እድሜያቸው 78 የሆኑት ፕሬዝዳንት ጌሌ፣ ይህንን ድል የተቀዳጁት የቀድሞው የገዢው ፓርቲ አባል በነበሩት ብቸኛ ተፎካካሪያቸው መሀመድ ፋራህ ሳማታር ላይ ሲሆን፣ ይህም ለ27 ዓመታት የቆየውን የስልጣን ዘመናቸውን ወደ ስድስተኛው ምዕራፍ እንዲያሸጋግሩ አስችሏቸዋል።

በ1999 እ.ኤ.አ. (1991 ዓ.ም) ስልጣን የያዙት ፕሬዝዳንቱ፣ በቆይታቸው ጅቡቲን የአለም አቀፍ የባህር ትራንስፖርት እና የወታደራዊ ስምሪት ማዕከል በማድረግ ረገድ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል።

በተለይም ለአለም አቀፍ ንግድ ቁልፍ በሆነው የባብ ኤል-መንደብ የባህር ወሽመጥ አቅራቢያ የምትገኘው ጅቡቲ፣ የአሜሪካን፣ የቻይናን እና የፈረንሳይን ግዙፍ የጦር ሰፈሮች በማስተናገድ በቀጠናው ፀጥታ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ አላት።

ፕሬዝዳንት ጌሌ የሀገሪቱን ወደቦች በማዘመን እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ወደብ አልባ እና ግዙፍ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላላቸው ሀገራት ዋነኛ የባህር በር እንዲሆኑ አድርገዋል። ይህ የግንኙነት መረብ ጅቡቲን በምስራቅ አፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል እንድትሆን አድርጓታል።

የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ ምርጫው በሰላም መጠናቀቁን አድንቀው ለፕሬዝዳንቱ የእንኳን ደስ አላችሁ መዕክት አስተላልፈዋል። በሌላ በኩል እንደ ‘ፍሪደም ሃውስ’ ያሉ አለም አቀፍ ተቋማት በሀገሪቱ ያለው የተቃዋሚዎች የፖለቲካ ተሳትፎ እጅግ የተገደበ መሆኑን በመጥቀስ የምርጫውን ሂደት ይተቻሉ።

ፕሬዝዳንት እስማኤል ኡመር ጌሌ ለቀጣይ አምስት ዓመታት የሚመሩት አዲሱ አስተዳደር፣ በቀይ ባህር አካባቢ ካለው የጸጥታ ስጋት እና ከቀጠናው የኢኮኖሚ ውድድር ጋር ተያይዞ ትልቅ ትኩረት እንደሚሰጠው ይጠበቃል።

Capital

2 months ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.