Logo
FastMereja
የስፖይና ቢፊዳ እና ሃድሮሴፈለስ በሽታን መከላከል የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ትኩረት ይፈልጋል ሲሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በዶ አሳስበዋል።

በአለም አቀፍ ለ14ኛ በኢትዮጵያ ለ7ኛ ጊዜ የተከበረውን የስፖይና ቢፊዳ እና ሃድሮሴፋለስ ቀን አስመልክቶ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ውይይት ተካሂዷል።

በዚሁ ሆፕ ኤስቢኤች የተሰኘ ግብረ ሰናይ ድርጅት ከምክር ቤቱ ጋር በመተባበር ለምክር ቤት አባላት ባዘጋጀው የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ ላይ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በዶ በሽታው በአገራችን ህፃናትን ብቻ ሳይሆን በአገሪቱም እድገት ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ያሳደረ በመሆኑ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው በመስራት ውጤት ማምጣት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።

ለውጤታማነቱ በየደረጃው ባሉ አካላት የሚኖረው ክትትልና ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ያሳሰቡት የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ ችግሩን መቀነስ ብቻ ሳይሆን ወደ ዜሮ ደረጃ ለማድረስ ቁርጠኛ መሆን ይገባል ብለዋል።

አክለውም የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴዎችም የጋራ እቅድ አውጥተው በመስራት የወጡ ህጎች ተግባራዊ መደረጋቸውን ማረጋገጥና ተጠያቂነትን ማስፈን ይገባቸዋል ሲሉም አስገንዝበዋል፡፡

የድርጅቱ መሰራችና ዋና ዳይሬከተር ወ/ሮ ቤዛ በሻህ በበኩላቸው ይህንን በህጻናት ላይ የሚከሰት የነርቭ ዘንግ ክፍተት እና የጭንቅላት ከመጠን በላይ የውሃ ክምችት በሽታን ለመከላከል በበጀትም በህግም መደገፍ እንደሚገባ ጠቁመው፤ በምክር ቤቱ በኩል ለጉዳዩ በተሰጠው ትኩረት መደሰታቸውንና ውይይቱም የበለጠ ለመስራት መነሳሳት የፈጠረላቸው መሆኑን ገልጸዋል።

በመድረኩም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ ከጤና ሚኒስቴርና ከኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የሚመለከታቸው ባለሙያዎችና አመራሮች ተገኝተዋል፡፡

7 months ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.