Logo
YenetaTube
እስራኤል የኢራን አፈ ጉባኤ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ልትገድላቸው ከምትፈልጋቸው ባለሥልጣናት ዝርዝር እንዲወጡ አደረገች

እስራኤል የኢራን የፓርላማ አፈ ጉባኤን እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን ልትገድላቸው ከምትፈልጋቸው የኢራን ባለሥልጣናት ዝርዝር ውስጥ ማስወጣቷን አንድ የፓኪስታን ባለሥልጣን ተናገሩ።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺን እና የአፈ ጉባኤ ሞሐመድ ባገር ጋሊባፍ ስም እስራኤል ከጥቃት ዒላማዋ ዝርዝር እንድታስወጣ ፓኪስታን በአሜሪካ በኩል ጥያቄ በማቅረቧ ተቀባይነት ማግኘቱን ባለሥልጣኑ ለሮይተርስ ዜና ወኪል ገልጸዋል።

" እስራኤል ሁለቱ ባለሥልጣናት የሚገኙባቸውን ስፍራዎች መረጃ ነበራት...እነሱም ሊገድሏቸው ይፈልጋሉ። ነገር ግን እኛ ለአሜሪካኖች እነዚህ ሰዎች ከተገደሉ ለድርድር የሚቀመጥ ሌላ ሰው እንደማይኖር ስለነገርናቸው እስራኤላውያኑ ዕቅዳቸውን እንዲተዉ አድርገዋል” ሲሉ ባለሥልጣኑ ተናግረዋል።
አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከከፈቱበት ዕለት አንስቶ በርካታ የኢራን ከፍተኛ ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ መሪዎች በእስራኤል ጥቃት የተገደሉ ሲሆን፣ እስራኤል ባለሥልጣናቱን ማደኗን እንደምትቀጥል በተደጋጋሚ ገልጻለች።

አንድ ወር ሊሞላው የተቃረበውን ጦርነት ለማስቆም በኢራን እና በአሜሪካ መካከል ሊካሄድ የታሰበውን ድርድር ፓኪስታን ታስተናግዳለች ተብሎ ይጠበቃል።
በዚህ ድርድር ላይ ኢራንን በመወከል በእስራኤል ዒላማ መደረጋቸው እየተነገረ ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ እንዲሁም በአሜሪካ በኩል ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ በዋናነት ይገኛሉ ተብሎ እየተጠበቀ ነው።

BBC

3 months ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.