Logo
Zehabesha
(ዘ-ሐበሻ ዜና) ትናንት ቅዳሜ፣ ሜይ 23 ከዋይት ሀውስ ቅጥር ግቢ ውጪ በጸጥታ ኃይሎች በተወሰደ አጸፋዊ እርምጃ የተገደለው ታጣቂ ማንነት ይፋ መደረጉን የተለያዩ የዜና አውታሮች ዘገቡ። ሲኤንኤን እና ሲቢኤስ ኒውስ ለምርመራው ቅርበት ያላቸውን ምንጮች ጠቅሰው እንደዘገቡት፣ ተጠርጣሪው የ21 ዓመቱ ናስር ቤስት መሆኑ ተረጋግጧል። ግለሰቡ በ17ኛው ጎዳና እና ፔንሲልቬንያ አቬኑ አካባቢ ወደሚገኘው የዋይት ሀውስ ቅጥር ግቢ በመጠጋት ከቦርሳው ውስጥ የጦር መሳሪያ በማውጣት ተደጋጋሚ ተኩስ መክፈቱ ተገልጿል።

የሲክሬት ሰርቪስ ፖሊሶች በወሰዱት ፈጣን አጸፋዊ እርምጃ ተጠርጣሪው በጥይት ተመትቶ ወደ አካባቢው ሆስፒታል ቢወሰድም ህይወቱ ማለፉ ተረጋግጧል። በተኩስ ልውውጡ ወቅት አንድ በአቅራቢያው የነበረ አላፊ መንገደኛ በጥይት ተመትቶ ከባድ ጉዳት የደረሰበት ሲሆን፣ በጸጥታ ኃይሎች ላይ ግን ምንም አይነት ጉዳት አልተመዘገበም። በዋይት ሀውስ ውጪ ባለው የጥበቃ ኬላ ላይ ከ10 እስከ 20 የሚገመቱ ጥይቶች የተተኩሱ ሲሆን፣ ክስተቱን ተከትሎ ዋይት ሀውስ እስከ ምሽቱ 6:45 p.m. አካባቢ ድረስ የደህንነት እገዳ ተጥሎበት መቆየቱን ትናንት በዘ-ሐበሻ ዜና መዘገባችን አይዘነጋም።

የኤቢሲ ኒውስ የዋይት ሀውስ ዘጋቢ ሴሊና ዋንግ፣ የተኩሱ ድምጽ ሲሰማ መሬት ላይ ስትወድቅ የሚያሳይ ቪዲዮ በማህበራዊ ትስስር ገጿ ላይ አጋርታ፣ ደርዘን የሚሆኑ ጥይቶች ሲተኮሱ ይሰማ እንደነበር እና በፍጥነት ወደ ጋዜጣዊ መግለጫ መስጫ ክፍሉ እንዲሮጡ ታዘው እዚያው ተጠልለው መቆየታቸውን በማስፈራር የነበረውን አስፈሪ ድባብ ገልጻለች።

በጥቃቱ ወቅት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በዋይት ሀውስ ውስጥ የነበሩ ቢሆንም ምንም አይነት አደጋ እንዳልደረሰባቸው የሲክሬት ሰርቪስ ቃል አቀባይ አረጋግጠዋል። ፕሬዝዳንቱ በ'ትሩዝ ሶሻል' ገጻቸው ባሰፈሩት መልእክት፣ ለአገሪቱ እጅግ የተከበረ ህንፃ ልዩ አባዜ በነበረውና የጥቃት ታሪክ ባለው ታጣቂ ላይ ለወሰዱት ፈጣን እና ሙያዊ እርምጃ ታላቁን የሲክሬት ሰርቪስ እና የህግ አስከባሪ አካላትን አመስግነዋል። ትራምፕ አክለውም፣ ይህ ክስተት ከዋይት ሀውስ የጋዜጠኞች እራት ግብዣ የተኩስ ጥቃት ከአንድ ወር በኋላ የተከሰተ መሆኑን አስታውሰው፣ የሀገሪቱ ብሄራዊ ደህንነት ለወደፊት ፕሬዝዳንቶች ይበልጥ ደህንነቱ የተጠበቀ ስፍራ መገንባትን አጥብቆ እንደሚጠይቅ አሳስበዋል።

በጸጥታ ኃይሎች የተገደለው ናስር ቤስት ከዚህ ቀደም ከዋይት ሀውስ ጋር የተያያዙ አሳሳቢ የህግ እና የስነ-ልቦና ሪከርዶች ነበሩት። በሰኔ 2025 በዋይት ሀውስ ምስራቃዊ ክፍል የተሽከርካሪ መግቢያን በመዝጋቱ ምክንያት አስገዳጅ በሆነ ሁኔታ ወደ አእምሮ ህክምና ማዕከል ገብቶ የነበረ ሲሆን፣ ወዲያውም በሀምሌ 2025 "እኔ ኢየሱስ ክርስቶስ ነኝ" በማለት ወደ ተከለከለው የዋይት ሀውስ ቅጥር ግቢ በመግባቱ በህገ-ወጥ ሰርጎ መግባት ወንጀል ታስሮ ነበር። በወቅቱም በተለያዩ የመግቢያ ኬላዎች ላይ እንዴት ሾልኮ መግባት እንደሚችል ሲጠያይቅ እንደነበር ሲክሬት ሰርቪስ አስተውሎ ነበር።

ከዚህ እስር በኋላ ወደ ዋይት ሀውስ አካባቢ እንዳይደርስ እገዳ የተጣለበት ቢሆንም፣ በነሐሴ ወር ፍርድ ቤት ሳይቀርብ በመቅረቱ የመያዣ ትዕዛዝ ወጥቶበት እንደነበር የፍርድ ቤት ሰነዶችን ጠቅሰው የዜና አውታሮቹ ዘግበዋል። ይህን የቅርብ ጊዜ ጥቃት በተመለከተ ከዋይት ሀውስ፣ ከሲክሬት ሰርቪስ እና ከኤፍቢአይ እስካሁን ተጨማሪ ማብራሪያ አልተሰጠም።

12 days ago

No replys yet!

Be the first to share what you think — your comment will appear here.